ህዳሴ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ዕጩዎችን ያቀረበ ፓርቲ ሆነ

“ምርጫ 2018 – ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት እና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት (ፓርላማ) ያቀረቧቸውን ዕጩዎች ቁጥር የተመለከተች ሲሆን፣ ህዳሴ ፓርቲ ለከተማው ምክር ቤት 155 እና ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 23 ዕጩዎችን በማቅረብ በድምሩ 178 ዕጩዎችን በማስመዝገብ ከፍተኛ ተወዳዳሪዎችን ያቀረበ ፓርቲ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል። በመከተልም፣ ብልጽግና ፓርቲ ለከተማው ምክር ቤት 134 እና ለፓርላማ 20፣ በድምሩ 154 እንዲሁም ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ለከተማው ምክር ቤት 132 እና ለፓርላማ 22፣ በድምሩ 152 ዕጩዎችን በማቅረብ በተወዳዳሪዎች ብዛት ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃን አግኝተዋል።

ህዳሴ ፓርቲ እና የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ ፓርቲ (ኢዜማ) ለ23ቱም የአዲስ አበባ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎች የሚወዳደሩ ሙሉ ዕጩዎችን ያቀረቡ ብቸኛዎቹ ፓርቲዎች ሆነዋል። ይሁን እንጂ አንድም የፖለቲካ ፓርቲ ለሁሉም የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ሙሉ 158 መቀመጫዎች የሚሆኑ ዕጩዎች አላቀረበም።

ለአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት እና የፓርላማ መቀመጫዎች ዕጩ ያቀረቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ብዛት 21 ሲሆን፣ ለአዲስ አበባ የፓርላማ ወንበሮች የሚወዳደሩ ሦስት እና ለከተማው ምክር ቤት የሚወዳደሩ 7 የግል ዕጩዎች መኖራቸው ተመላክቷል። [ምርጫ 2018 – ኢትዮጵያ ኢንሳይደር]