ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ውስጣዊ ክፍፍሉ ሳይቋጭ፣ ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ እየተዘጋጀ መሆኑ ተገለጸ
ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ (ባልደራስ) ፓርቲ በዘንድሮው 7ኛው ጠቅላላ ሀገር አቀፍ ምርጫ “በውስጥ በነበሩ መከፋፈሎች” ውስጥ ሆኖም ለምርጫ እየተዘጋጀ መሆኑን የፓርቲው ፕሬዚዳንት አቶ አምሃ ዳኜ ለ“ምርጫ 2018 - ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ገለጹ። ፕሬዚዳንቱ በውስጣዊ መከፋፈሉ ሳቢያ በበቂ ሁኔታ ዝግጅት ማድረግ ባይችሉም፣ ፓርቲው 300 የሚሆኑ ዕጩዎችን ለምርጫ ውድድር አስመዝግቧል ብለዋል።
“ከዓመት በላይ ስንካሰስ የቆየን በመሆኑ፣ ቢሯችን በላያችን ላይ በመፍረሱ፣ እንዲሁም የባንክ አካውንታችን በመዘጋቱ፣ በዚሁ ሁሉ ችግር ውስጥ ዝግጅት እያደረግን ነው” ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ ባልደራስ በውስጥ ክፍፍሉ ምክንያት፣ ከውጪ ገንዘብ ይልኩለት የነበሩት እና በቀድሞው የፓርቲው ፕሬዚዳንት የተቋቋመው የባልደራስ የሰሜን አሜሪካ ደጋፊ የሚባለው ቡድን አባላት ድጋፋቸውን ካቋረጡ ከአንድ ዓመት በላይ እንደሆናቸውም ጨምረው ገልጸዋል። አቶ አምሃ ዳኜ፣ በክፍፍሉ ሳቢያ ወደ “ሦስት ሚሊዮን የሚጠጋ ገንዘብ” በፍርድ ቤት እንደታገደባቸውም ገልጸዋል።
ይሁን እንጂ፣ የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር በቃሉ አጥናፉ፣ የክፍፍሉ መንስዔ የድርጅቱ ፕሬዚዳንት እና አፈ ጉባዔ፣ ምልዓተ ጉባኤው ያልተሟላበት የብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ በማድረግ የአመራር ለውጥ በማድረጋቸው መሆኑን በመግለጽ ተችተዋል።
አቶ አምሃ ግን ልዩነቱ የተፈጠረው “በውጭ ያሉት ደጋፊዎቹ እና በሀገር ውስጥ...

